የትግራይ ኃይሎች ከሐምሌ 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ተቆጣጥረዋቸው በነበሩ አካባቢዎች፤ ከጦር እና በሰብዓዊነት ላይ ከሚፈጸም ወንጀል ጋር የሚስተካከሉ ወንጀሎችን ስለመፈጸማቸው የሚያመለክቱ ማስረጃዎች መኖራቸውን የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ዛሬ ይፋ ባደረገው ሪፖርት አመልክቷል። ከ15 ወራት በፊት በትግራይ የተቀሰቀሰው ጦርነት ወደ አማራ እና አፋር ክልሎች ተሸጋግሮ ከፍተኛ ሰብዓዊ እና ቁሳዊ ቀውስን አስከትሏል። በዚህ ጦርነት ተሳታፊ የሆኑት የፌደራሉ መንግሥት ጦር፣ የአማራ ክልል ኃይሎች፣ የኤርትራ ሠራዊት እና የህወሓት ኃይሎች በከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ተጠያቂ ስለመሆናቸው በተለያዩ ወገኖች በተደጋጋሚ ሲከሰሱ ቆይተዋል።
አምነስቲ ኢንተርናሽናል የትግራይ ኃይሎች በአማራ ክልል ከተሞች የሚገኙ በርካታ ንጹሃን ሰዎችን ሆነ ብለው መግደላቸውን፣ ሴቶች እና ታዳጊዎችን አስገድደው በቡድን መድፈራቸውን እንዲሁም የግል እና የሕዝብ ንብረት ማውደማቸውን ሪፖርቱ አስታውቋል። ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ቡድን ከህወሓት ጋር ግነንኙነት ያላቸው ታጣቂዎች በጭና እና ቆቦ ከተሞች እንዲሁም በአካባቢው በሚገኙ ስፍራዎች ላይ ጥቃት ያደረሱት ከነሐሴ 2013 ዓ.ም. አጋማሽ እስከ መስከረም 2014 ዓ.ም. መጀመሪያ ባሉት ጊዜያት ነው ብሏል። ጨምሮም በአካል ላይ ከሚደርሱት ጥቃቶች በተጨማሪ የግድያ ማስፈራሪያዎች፣ ብሔር ተኮር ስድቦች እና ማንቋሸሾች በተጠቂዎች ላይ ሲደርሱ ነበር ብሏል።
የትግራይ ኃይሎች በቆቦ ከታጣቂ ነዋሪዎች እንዲሁም ከሚሊሻዎች የገጠማቸውን መገዳደር ለመበቀለ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የበቀል እርምጃ ሲወስዱ ነበር ብሏል አምነስቲ በሪፖርቱ። የትግራይ ኃይሎች ተቆጣጥረዋቸው በነበሩ በእነዚህ የአማራ ክልል አካባቢዎች ዓለም አቀፍ መሠረታዊ የሰብዓዊ ሕጎችን አለማክበራቸውንም አምነስቲ ገልጿል። የአምነስቲ የምሥራቅ አፍሪካ እና ግሬት ሌክስ ምክትል አካባቢ ዳይሬክተር ሳራ ጃክሰን የትግራይ ኃይሎች በስፋት የአስገድዶ መድፈር ጥቃቶችን፣ ግድያዎችን እና ከሆስፒታል ሳይቀር ዝርፊያ መፈጸማቸውን ገልጸዋል። ምክትል ዳይሬክተሯ የህወሓት አመራሮች በዚህ ወንጀል ተሳታፊ ሳይሆኑ አይቀሩም የተባሉ አባላቱን ከጦሩ እንዲያስወግዱም ጠይቀዋል።
የቆቦ ርሸና
አምነስቲ በሰሜን ምሥራቅ አማራ በምትገኘው ቆቦ ከተማ የትግራይ ኃይሎች በአማራ ሚሊሻ እና በታጣቂ ገበሬዎች የደረሰባቸውን ሽንፈት ለመበቀል ያልታጠቁ ሲቪል ሰዎችን ሆነ ብለው ገድለዋል ብሏል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል 27 የዓይን መስክሮችን እና ከጥቃቱ የተረፉ ሰዎችን ማነጋገሩን በሪፖርቱ አመልክቷል። ከእነዚህ ምስክሮች መካከል 10 የከተማዋ ነዋሪዎች የህወሓት ኃይሎች ጳጉሜ 04/2013 ዓ.ም. ዘመዶቻቸውን እና ጎረቤቶቻቸውን ከመኖሪያ ቤት ፊት ለፊት ላይ አውጥተው መረሸናቸውን ነግረውኛል ብሏል በሪፖርቱ።
“መጀመሪያ ወንድሜ ታደሰ ላይ ተኮሱ . . . እዚያው ሞተ። ሌላኛው ወንድሜ እና አማቼ ለማምለጥ ሲሞክሩ ከጀርባቸው ተመተው ተገደሉ. . . እኔን ግራ ትከሻዬ ላይ መቱኝ . . . ወድቄ የሞትኩ አስመሰልኩ” በማለት ከጥቃቱ በሕይወት የተረፈው ግለሰብ ለአምነስቲ ኢንተርናሽናል ተናግሯል።

የቆቦ ከተማ ነዋሪዎች የአካባቢው ነዋሪዎች እና የቀን ሠራተኞች 12 ተጨማሪ አስክሬኖችን ማግኘታቸውን ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ተናግረዋል። እነዚህ ነዋሪዎች ያገኟቸው አስክሬኖች ርሸና በሚመስል መልኩ ጨንቅላታቸውን፣ ጀርባቸውን፣ ደረታቸውን በጥይት የተመቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪም እጃቸው ወደ ኋላ ተጠንፍሮ የተገደሉ ሰዎች አስክሬን ማንሳታቸውንም ጨምረው ተናግረዋል።
“የመጀመሪያዎቹ አስክሬኖች ያየነው ከትምህርት ቤት አጥር አቅራቢያ ነበር። 20 አስክሬኖች በውስጥ ልብስ ብቻ ነበሩ። . . . . አብዛኛዎቹ ጭንቅላታቸው ኋላ ላይ የተመቱ ናቸው። አንዳንዶቹ ደግሞ ከጀርባቸው። ጨንቅላታቸው ከኋላ የተመቱ ሰዎችን መለየት አልተቻለም ምክንያቱም በጥይት የፊታቸው አካል ተበትኗል” በማለት አንድ ነዋሪ ለአምነስቲ ተናግሯል።
አምነስቲ የሳተላይነት ምስሎችን ተመልክቼ በርካታ ሰዎች በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት መቀበራቸውን አረጋግጫለሁ ብሏል። ይህም ነዋሪዎች በቃለ መጠይቅ ወቅት ከሰጡት ምስክርነት ጋር እንደሚመሳከር አምነስቲ ገልጿል። የሰላማዊ ሰዎች ግድያ፤ አልያም የተማረኩ እስረኞች፣ እጅ የሰጡ ወይም የቆሰሉ ወታደሮችን መግደል ከጦር ወንጀል ጋር እንደሚስተካከል ምናልባትም በሰብዓዊነት ላይ የሚፈጸም ወንጀል ሊሆን እንደሚችል አምነስቲ በሪፖርት አመልክቷል።
ጾታዊ ጥቃት በጭና
ከሐምሌ 2013 ዓ.ም. ጀምሮ በጭና እና በዙሪያዋ እድሜያቸው 14 የሚሆኑ ሴት ታዳጊዎችን ጨምሮ የትግራይ ኃይሎች በርካታ ሴቶችን በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ መድፈራቸውን እና አስገድደው ምግብ እንዲያበስሉላቸው ማድረጋቸውን አምነስቲ በሪፖርቱ አትቷል። አምነስቲ ያነጋገራቸው 14 የጾታዊ ጥቃት ሰለባዎች በቡድን፤ አንዳንዶቹ ልጆቻቸው ፊት መደፈራቸውን ተናግረዋል። አንዲት የ7ኛ ክፍል ተማሪ እና 14 ዓመት ታዳጊ ከእናቷ ጋር በመኖሪያቸው ድር-ባሕር በትግራይ ኃይሎች መደፈሯን ለአምነስቲ ተናግራለች።
ይህች ታዳጊ “ረፋድ 5 ሰዓት አካባቢ መሳሪያ የያዙ ሁለት ወጣቶች ወደ ቤታችን ሲመጡ ከእናቴ እና ከአያቴ ጋር ነበርኩ። አንደኛው የወታደር ልብስ ነው የለበሰው ሌላኛው ደግሞ የሲቪል ልብስ። ትግርኛ እና አማርኛ እየቀላቀሉ ነው የሚያወሩት። ‘ቤተሰቦቻችን ተደፍረዋል አሁን እናንተን የምንደፍርበት ተራ ነው’ አሉን። አንደኛው ከቤት ውጪ እኔን ደፈረኝ። ሌላኛው ደግሞ ቤት ውስጥ እናቴን ደፈረ። እናቴ አሁን ታማለች። . . . ምን እንደተፈጠረ አናወራም” ስትል ለአምነስቲ ተናግራለች። የ29 ዓመቷ ሰላም ለ15 ሰዓታት በዘለቀ ቆይታ እንዴት 4 የትግራይ ወታደሮች እየተፈራረቁ አስገድደው እንደደፈሯት ለአምነስቲ ተናግራለች።
የንብረት ዝርፊያ
በቆቦ እና ጭና ከተማ አካባቢዎች የትግራይ ኃይሎች የግል እና የመንግሥት ንብረቶችን ስለመዝረፋቸው እና ስለማውደማቸው የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪው ድርጅት በሪፖርቱ ላይ ጠቅሷል። በጤና ተቋማት ላይ የደረሰው ውድመት እና ዝርፊያ ጾታን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች የደሰረባቸውን ሴቶችን ጨምሮ ሌሎች የጤና እክል የገጠማቸው ሰዎች ሕክምና እንዳያገኙ ምክንያት መሆኑንም ሪፖርቱ አመልክቷል። ከዚህ ቀደም ቢቢሲ በቆቦ ከተማ የሚገኙ የመንግሥት ተቋማት ሙሉ በሙሉ መዘረፋቸውን ከከተማዋ ነዋሪዎች ሰምቶ ነበር።
ነዋሪዎች ዘረፋው ከመንግሥት ተቋማት እና ከግለሰብ ንብረት የዘለለ እንደሆነም ይናገራሉ። “እንኳን የሱቅ እቃ ሰው ያልገባባቸው የማኅበር ቤቶች ቆርቆሮ እየተገነጠሉ ተወስደዋል” ብሏሲል አንድ ነዋሪ የነበረውን ሁኔታ ገልጿል። በአማራ ክልል ውስጥ በሚገኙት በጭናና በቆቦ ውስጥ የተፈጸሙትን ከባድ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በተመለከተ ዓለም አቀፉ ተቋም አምነስቲ ባወጣው ሪፖርት ላይ ክስ የቀረበበት ህወሓት አስካሁን ያለው ነገር የለም።
ምንጭ – ቢቢሲ