የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የምርጫ ጉዳዮች ችሎት፣ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. በተካሄደው ስድስተኛው አገራዊ ምርጫ በ28 የምርጫ ክልሎች ላይ የተካሄደው ምርጫ፣ የምርጫ ሕጉንና ማስፈጸሚያ መመርያዎችን የጣሰ መሆኑን ጠቅሶ ባቀረበው ክስ ላይ ነሐሴ 12 ቀን 2013 ዓ.ም. ከምርጫ ቦርድ ጋር እንዲከራከሩ አድርጎ ውሳኔ ለመስጠት ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ፡፡

ክርክሩን ከኢዜማ በኩል የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ የሽዋስ አሰፋና ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በኩል ደግሞ የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ አቶ አየለ ውብሸት በችሎት ተገኝተው ክርክራቸውን አሰምተዋል፡፡ አቶ የሽዋስ ባቀረቡት ክርክር ፓርቲያቸው (ኢዜማ) ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. በተካሄደው አገራዊ ምርጫ፣ በ28 የምርጫ ክልሎች የምርጫ ሕግ ጥሰት መፈጸሙን በመግለጽ ለምርጫ ቦርድ ምርጫው እንዲደገም 156 ገጽ የምሥልና የሰነድ ማስረጃ አስደግፎ አቤቱታ ቢያስገባም፣ ቦርዱ ሳይቀበለው መቅረቱን አስረድተዋል፡፡ ቦርዱ በምርጫ ወረቀት ኅትመት ላይ የዕጩ ተወዳዳሪዎችን ፎቶ ባለማካተቱ አባላቱ ለመወዳደር አለመቻላቸውንም አክለዋል፡፡

የምርጫ የድምፅ ኮሮጆ አከፋፈትን በተመለከተ የፓርቲው ታዛቢዎች ባልተገኙበት መከፈቱ አግባብ አለመሆኑን፣ በቅሬታው ላይ አካቶ ማቅረቡንም ሊቀመንበሩ ጠቁመዋል፡፡ አቶ የሽዋስ ጨምረውም በድምፅ አሰጣጥ ሒደት ላይ መራጮች ነፃ ሆነው መምረጥ ሲገባቸው፣ መራጮችን በማሸማቀቅ ገዥውን ፓርቲ እንዲመርጡ መደረጉን፣ ታዛቢዎቹ (ወኪሎቹ) እንዳይከታተሉ መደረጋቸውንና በአጠቃላይ የተፈጸመበት ድርጊት የምርጫ ሕጉንና መመርያዎቹን የተከተለ አለመሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

ኢዜማ ሰኔ 18 ቀን 2013 ዓ.ም. ለቦርዱ ቅሬታውን ከ156 ገጽ የሰነድና የምሥል ማስረጃ ጋር ቢያቀርብም፣ በቦርዱ ማስረጃውን ሳይመረምር በደፈናው ውሳኔ መስጠቱ አግባብ አለመሆኑን በመጥቀስ አቶ የሽዋስ የቃል ክርክራቸውን አቅርበው፣ ፍርድ ቤቱ አቤቱታውን ተመልክቶ አቤቱታ የቀረበባቸው 28 ምርጫ ክልሎች ምርጫ እንዲደገም ውሳኔ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡

ኢዜማ ላቀረበው የክስ አቤቱታ ምላሽ የሰጡት የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ውብሸት ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት፣ ኢዜማ ከመጀመርያው ጀምሮ ያቀረበው የቅሬታ አቀራረብ ሥርዓትን የተከተለ አይደለም፡፡ ኢዜማ አቤቱታ ባቀረበባቸው ነጥቦች የትና በማን ጥሰት እንደተፈጸመ ዝርዝር ማስረጃ አቅርብ ቢባልም፣ ያቀረበው በስድስቱ የምርጫ ክልሎች ላይ ብቻ እንደሆነ፣ ሁለቱ የምርጫ ክልሎች ባዶ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

ኢዜማ በአርባ ምንጭና ሌሎች አካባቢዎች ተፈጸመ ላለው ጥሰት ምስክር እንዲያቀርብ ቦርዱ ጠይቆት አለማቅረቡን፣ ለጋምቤላው ግን በዕጩ የሕግ ማዕቀፍ መሠረት መልስ እንደተሰጠው አስረድተዋል፡፡ የዕጩዎችን ፎቶ በሚመለከት ቦርዱ በወቅቱ የፓርቲዎች የዕጩ ቁጥር አጠቃላይ ዝርዝር ማሳየቱንና በተለያዩ አማራጮች እንዲገለጽ ማደረጉን፣ ኢዜማ በወቅቱ ዕድል እያለው ሳያቀርብ ቀርቶ ምርጫው ከተደረገ በኋላ አቤቱታ ማቅረቡ ተገቢ እንዳልሆነ አክለዋል፡፡

በአጠቃላይ ኢዜማ ጥሰት ተፈጽሟል ባለው አቤቱታ ላይ የት? መቼ? እና በማን? የሚለውን ዝርዝር ማስረጃ አላቀረበም ሲሉ አቶ ውብሸት ገልጸዋል፡፡ የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው ፍርድ ቤቱ ውሳኔ መዝገቡን መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለነሐሴ 18 ቀን 2013 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር

selegna

By selegna

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *