የትግራይ ኃይሎችን እየመሩ እንደሆነ የሚነገርላቸው ጄነራል ጻድቃን ገ/ትንሳይ በአፋር እና አማራ ክልሎች ጥቃት የከፈቱት በፌደራሉ መንግሥት ላይ ጫና ለማሳደር መሆኑን ለቢቢሲ ተናገሩ።
ጄነራል ጻድቃን ከጦር ኦፕሬሽኖቻቸው ዓላማዎች አንዱ የፌደራሉ መንግሥት የትግራይ ኃይሎች የተኩስ አቁም ለማድረግ ያስቀመጡትን ቅድመ ሁኔታዎች ተቀብሎ ወደ ፖለቲካዊ ውይይት እንዲመጣ ለማስገደድ መሆኑን ከቢቢሲ ‘ኒውስ አዎር’ ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል።
የ68 ዓመቱ ጄነራል በቅርቡ ከሌሎች የህወሓት ከፍተኛ አመራሮች ጋር በአገር ክህደት ክስ ተመስርቶባቸዋል። ህወሓትም ከጥቂት ወራት በፊት በአገሪቱ ፓርላማ “አሸባሪ” ተብሎ መፈረጁ ይታወሳል።
ጄነራል ጻድቃን በአሁኑ ወቅት “በትግራይ ክልላዊ መንግሥት ሥር የተቋቋመው ማዕከላዊ ዕዝ [ሴንትራል ኮማንድ] አባል ነኝ” ያሉ ሲሆን ትናንት እሁድ ከቢቢሲ የእንግሊዝኛው ክፍል ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተዋል።
ቢቢሲ፡ ከሰሞኑ በአፋር ክልል በኩል ጥቃት መክፈታችሁ ተሰምቷል። ለምንድነው በዚያ የአገሪቷ ክፍል በኩል ጥቃት የሰነዘራችሁት?
ጄነራል ጻድቃን፡ ጥቃት ብሎ መጥራት ይከብደኛል። ለማንኛውም እንደ ሚታውቀው መላው ትግራይ በጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ ተዘግቶ ነው ያለው። ይህን መዘጋት (ብሎኬጅ) መስበር አለብን። ይህን ለማድረግ አንዱ መንገድ የአፋር አካባቢ ነው። ምክንያቱ ጂቡቲን ከትግራይ የሚያገናኘው ይህ አካባቢ ነው። መዘጋቱ እስካለ ድረስ ይህን መዘጋት መስበር አለብን። የምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎችም ይህንኑ ታላሚ ያደረጉ ናቸው።
ሁለተኛው ነገር እንደሚታውቀው የተኩስ አቁም ለማድረግ የራሳችንን ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጠናል። ከትግራይ መንግሥት ለተሰጠው የተኩስ አቁም ቅድመ ሁኔታ አግባብ የሆነ ምላሽ አልተሰጠውም ስለዚህ ጫና ማሳደር አለብን።
ቢቢሲ፡ በአሁኑ ወቅት የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ትግራይ እየገባ ነው?
ጄነራል ጻድቃን፡ ለጊዜው እየገባ አይደለም።
ቢቢሲ፡ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ትግራይ ሊገባ የሚችልበት ሌላ መተላለፊያ አለ?
ጄነራል ጻድቃን፡ አዎ። ምዕራብ ትግራይ። ትግራይን ከሱዳን የሚያገናኛው ሌላኛው አቅጣጫ ይህ ነው።
ቢቢሲ፡ በእሱ አቅጣጫ እርዳታ እየገባ ነው?
ጄነራል ጻድቃን፡ አይ። ለጊዜው እየገባ አይደለም።
ቢቢሲ፡ ‘ለጊዜ እየገባ አይደለም’ ነው ያሉት በሱዳን ድንበር በኩል እርዳታ እንዲገባ ምን መሆን አለበት?
ጄነራል ጻድቃን፡ አሁን ስልጣን ላይ ካለው የአዲስ አበባው መንግሥት ጋር ስምምነት መደረስ አለበት፤ አልያም ደግሞ መዘጋቱን በመስበር እርዳታ ወደ ትግራይ እንዲመጣ ማድረግ አለብን። ከሁለት አንዱ።
ቢቢሲ፡ በአሁኑ ወቅት በትግራይ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስ እንዴት ይመለከቱታል?
ጄነራል ጻድቃን፡ እጅግ አስቀያሚ እንደሆነ አውቃለሁ፤ ይቅርታ ቢሆንም ግን በዚህ ጉዳይ ላይ ዝርዝር ማብራሪያ መስጠት ያለብኝ ሰው አይደለሁም። በጉዳዩ ላይ ከሚሰሩ ሰዎች ዝርዝር መረጃ ማግኘት ትችላለህ።
ቢቢሲ፡ አሁን ደግሞ ወደ አማራ ክልል እንሂድ። በአማራ ክልል ላይስ ለምንድነው ጥቃት የምትሰነዝሩት?
ጄነራል ጻድቃን፡ በአሁኑ ወቅት የምናካሂዳቸው ሁሉም ወታደራዊ እንቅስቃሴዎቻችን ሁለት ዋና ዓላማዎች ነው ያሏቸው። የመጀመሪያው በመላው የትግራይ ሕዝብ ላይ የተጣለውን መዘጋት ለማስከፈት ነው።
ሁለተኛው ያስቀመጥነው የተኩስ አቁም መንግሥት እንዲቀበል ለማስገደድ ነው። ከዚያ አሁን በኢትዮጵያ ላለው ሁኔታ የፖለቲካ መፍትሄ ለማምጣት ውይይት ይደረጋል።
ቢቢሲ፡ ይገባናል የምትሉት መሬት በአማራ ክልል ስለተወሰደባችሁ አይደለም በአማራ ክልል ላይ ጥቃት የከፈታችሁት?
ጄነራል ጻድቃን፡ እውነት ነው። አሁንም ቢሆን የአማራ ሚሊሻዎች ምዕራብ ትግራይ ላይ ይገኛሉ። ይህ ግን ለተወሰደብን እርምጃ ምላሽ ለመስጠት አይደለም። በወታደራዊ እርምጃዎች ግዛቶቻችንን መልሰን እንደምናገኝ ምንም ጥርጥር የለም።
ግን የአሁኑ ዋነኛ ዓላማችን የተዘጋውን ማስከፈት እና የተኩስ አቁም ቅድመ ሁኔታዎችን መንግሥት እንዲቀበል ጫና ማሳደር ነው።
ቢቢሲ፡ የኢትዮጵያ መንግሥት የተናጠል ተኩስ አቁም አድርጊያለሁ ብሏል። እናንተ የተኩስ አቁም ለማድረግ ቅድመ ሁኔታዎችን ዘርዝራችኋል። ከእነዚህ ነጥቦች መሠረታዊ የሚባሉት የትኞቹ ናቸው? የትኞቹ ቅድመ ሁኔታዎች ተቀባይነት ቢያገኙ ነው የትግራይ ተዋጊዎች ነፍጣቸውን የሚያወርዱት?
ጄነራል ጻድቃን፡ የትግራይ መንግሥት ግልጽ አድርጎታል። አጠቃላይ ሁኔታውን በሁለት ከፍለን ነው የምንመለከተው። የመጀመሪያው በጦርነቱ ተሳታፊ የሆኑት ወገኖች የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ መድረስ ነው።
የተኩስ አቁም ለማድረግ ደግሞ ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጠናል። ይህም ለሕዝብ ይፋ ሆኗል። ከቅድመ ሁኔታዎቹ መካከል የተዘጋው መንገድ ክፍት መሆን አለበት፤ ሁሉም አገልግሎቶች መጀመር አለባቸው፤ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ትግራይ መግባት አለበት።
ሁለተኛው ደግሞ በአዲስ አበባ የሚገኙ የትግራይ ተወላጆችን ማዋከብ መቆም አለበት። ሦስተኛው የፖለቲካ እስረኞች መፈታት አለባቸው።
የትግራይ ተወላጅ የሆኑ የፖለቲካ እስረኞችን ብቻ ሳይሆን ሁሉም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ተሳታፊ የሆኑት መፈታት አለባቸው። ይህ የመጀመሪያው አጠቃላይ ሁኔታውን የምንመለከትበት አንዱ ነው።
በአሁኑ ወቅት ጠቅላይ ሚንስትሩ የተኩስ አቁሙ ላይ በሚስጥር እንድንወያይ ተዓማኒነት ያላቸው መልዕክቶች እየደረሱን ነው። እኛ ይህ ለሕዝብ ይፋ መሆን አለበት እያልን ነው። ቅድመ ሁኔታዎቹም መከበር አለባቸው።
በሁለተኛ ደረጃ የተኩስ አቁሙ ስምምነት ከተደረሰ በፍጥነት ሁሉን አቀፍ ፖለቲካዊ ውይይት ተደርጎ የኢትዮጵያን የፖለቲካ የወደፊት ዕጣ ለመወሰን የሽግግር ሂደት መጀመር አለበት።
ቢቢሲ፡ ትግራይ አንድ ክልል ነች። እንዴት ነው አንድ ክልል በመላው የኢትዮጵያ ዕጣ ፈንታ ላይ ውሳኔ የሚሰጠው? አንድ ክልል ናችሁ?
ጄነራል ጻድቃን፡ እኛ የኢትዮጵያን የወደፊት ፖለቲካ እንወስናለን አላልንም። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ዕጣ ለመወሰን ዋና ከሚባሉት የፖለቲካ ኃይሎች ጋር እኛ አንድ አካል እንሆናለን ነው ያልኩት።
ቢቢሲ፡ በመንግሥት ታስረዋል ከተባሉት በርካታ ሰዎች መካከል አንዱ የእርሶ ልጅ ሰናይ መሆኑን ተሰምቷል።
ጄነራል ጻድቃን፡ ተበድሏል። አሁን ግን ከእስር ውጪ ነው። ከኢትዮጵያ ውጪ ነው ያለው። በአዲስ አበባ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በማንነታቸው ብቻ ለእስር እየተዳረጉ ነው። እሱም የዚህ ተጠቂ ነው።
ቢቢሲ፡ ትግራይ ከኢትዮጵያ ጋር ምን አይነት ግንኙነት ይኖራታል ብለው ያስባሉ? ራሷን ያቻለች አገር መፍጠርን ነው የምታስቡት ወይስ እንደ ከዚህ ቀደሙ በማዕከላዊው መንግሥት የበላይነትን መያዝ ትፈልጋላችሁ?
ጄነራል ጻድቃን፡ አንደኛውን አማራጭ እንደ አማራጭ እንመለከተውም። ሁለተኛውን በተመለከተ ግን ሕዝቡ ራሱ ነጻ አገር መሠረተ ወይም ሌላ የሚለው በትግራይ ሕዝብ የሚወሰን ነው የሚሆነው።

ቢቢሲ፡ ነጻ አገር ለመሆን በትግራይ ሕዝበ ውሳኔ ይካሄዳል እያሉ ነው?
ጄነራል ጻድቃን፡ ነጻነት ወይም በፌደራል መንግሥቱ ስር መቀጠል ከሚለው ጉዳይ በፊት የተኩስ አቁም መደረግ አለበት። ከዚያ በኢትዮጵያ ያሉ የፖለቲካ ኃይሎችን ያካተተ ውይይት ቀድሞ መካሄድ አለበት። የፖለቲካ ስምምነት ከተደረሰ በኋላ ሕዝቡ ይመክርበታል።
ቢቢሲ፡ በዚህ ጦርነት በሁሉም በኩል በርካቶች ሕይወታቸውን አጥተዋል። ንጹሃን ዜጎች ተገድለዋል። እንደው ይህ ጦርነት አያስቆጨዎትም?
ጄነራል ጻድቃን፡ ይህ ጦርነት መደረግ ያልነበረበት ጦርነት ነው። በትግራይ እና አዲስ አበባ ያሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት አነጋግሬ ጦርነቱ እንዳይካሄድ እንደ አንድ ዜጋ ጥረት አድርጊያለሁ። የአዲስ አበባ ባለስልጣናት ሰላማዊ የፖለቲካ መፍትሄ መስጠት አልፈለጉም። የፖለቲካ ፍላጎታቸውን ለመጫን ፈልገዋል። ይህ ጦርነት መከስት አልነበረበትም ይቆጨኛል። ጦርነቱን ማስቀረት ይቻል ነበር። በተመሳሳይ ሰዓት የትግራይ ሕዝብ በመዋጋቱ ደስተኛ ነኝ። በአሁኑ ወቅት የትግራይ ሕዝብ የሚገባውን መጠየቅ የሚችልበት አቋም ላይ ነው ያለው።
ቢቢሲ፡ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ጦር በአሁኑ ወቅት ትግራይ ውስጥ ይገኛሉ?
ጄነራል ጻድቃን፡ አዎ። የኤርትራ ጦር በትግራይ አለ። የኢትዮጵያ ፌደራል ጦር እና የክልል ኃይሎች በምዕራብ ትግራይ ይገኛሉ። በስምምነት ይወጣሉ አልያም እናስወጣቸዋለን።
ቢቢሲ፡ ዓለም ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ ሰላም አምጥተዋል ብሎ የኖቤል የሰላም ሽልማት መስጠቱ ስህተት ነው ብለው ያስባሉ?
ጄነራል ጻድቃን፡ ተግባሩ ይመሰክራል። እሱ እንዲህ ነው ብዬ እኔ ፍርድ ልሰጥ አልፈልግም። ባለፉት ሦስት ዓመታት የሰራቸው ሥራዎች ካልመዘኑት ዓለም ምን ምስክር ይፈልጋል?
ምንጭ – ቢቢሲ