ላለፉት ስምንት ወራት በትግራይ ክልል ከሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ጋር ሲደረግ የነበረውን ጦርነት በመተው ከክልሉ መውጣቱ ሲዋጋው ከነበረው ሕወሓት ይልቅ የአገሪቱ ሥጋት የሆኑ ሌሎች ችግሮች አሉና በእነሱ ለማተኮር ነው ሲል መንግሥት አስታወቀ፡፡

ሰኔ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመሰብሰቢያ አዳራሽ ለጋዘጠኞች መግለጫ የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሬድዋን ሁሴን (አምባሳደር) እና የመከላከያ ሠራዊት፣ የሠራዊት ግንባታ አስተባባሪ ሌተናል ጄኔራል ባጫ ደበሌ አሁን ኢትዮጵያ ሕወሓት ባለበት አቅም የብሔራዊ ደኅንነት ሥጋት ስላልሆነና ለሌሎች ሥጋቶች ዝግጅት ለማድረግ እንዲቻል በማለም ሠራዊቱ ከትግራይ እንዲወጣ ተደርጓል ብለዋል፡፡

በተለይ መቐለ አስቀድሞ የነበራትን የስህበት ማዕከልነት አሁን ላይ አጥታለችና መቐለ መቆየትም ሆነ መልቀቅ ከወታደራዊ ጠቀሜታው አንፃር ሌሎች አካባቢዎችን ከመያዝ የተለየ አይደለም ያሉት ሌተናል ጄኔራል ባጫ፣ አስፈላጊ ከሆነ በሦስት ሳምንታት ወይም ከዚያ ባነሰ ጊዜ ተመልሰን መቐለ አንገባለን ብለዋል፡፡ ይሁንና፣ ጥፋቱና የሚወሰደው ዕርምጃ ከመጀመርያው የበለጠ ይሆናልም ሲሉ አሳስበዋል፡፡

ጄኔራሉ በሰጡት ማብራሪያ የሚፈለጉት ጄኔራሎች ከ17፣ የሲቪል አመራሮች ደግ ከ12 አይበልጡም ያሉ ሲሆን፣ ለእነዚህ ደግሞ የተሰማራው ኃይል ከ50 ሺሕ በላይ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ ስለዚህም ይኼ ወታደሩን ለማስወጣት የተላለፈው ፖለቲካዊ ውሳኔ ከወታደራዊ ትርፍና ኪሳራ አንፃር ዋጋው ከፍተኛ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሥጋት እንዳይሆን ተደርጓል የተባው ሕወሓትም ከትግራይ እንደይወጣ ይደረጋል ያሉት ጄኔራሉ፣ የሠራዊቱ ትኩረት አሁን ወደ ሌላ ሥጋቶች እንደሚሆንም ጠቁመዋል፡፡

‹‹ሕወሓት ኢትዮጵያን የሚያሠጋ ጉዳት አያደርስም፤›› በማለትም ተናግረዋል፡፡ አምባሳደር ሬድዋን በበኩለቸው ጦርነቱ ለስምንት ወራት ሲካሄድ 100 ቢሊዮን ብር ገደማ ወጪ እንደተደረገ በመግለጽ፣ ይኼም አገራዊ የኢኮኖሚ አቅማችን ላይ ጉዳት አድርሷል ብለዋል፡፡ ‹‹የወደመው ሀብት በጣም ብዙ ነው፡  የወጣው ወጪም የመከላከያን ወጪ ሳይጨምር ነው፡፡ ይኼም የትግራይን ዓመታዊ በጀት ለአሥራ ምናምን ዓመታት መሸፈን የሚችል ነው›› በማለት፣ የትግራይ ክልል ዓመታዊ በጀት ስምንት ቢለዮን ብር መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡

ኢትዮጵያ ለውጭ ጥቃት የተጋለጠችበት ሁኔታ መፈጠሩን የገለጹት አምባሳደር ሬድዋን፣ በምዕራብ በኩል ድንበር ተወርሯል፣ የኢትዮጵያን ውስጣዊ ችግር በማየትም ወታደራዊ ልምምድ በማድረግ ጦርነት እየተደገሰላት እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በመተጨማሪም፣ ከዚህ በላይ ከተቆየ የሚጎዳው ሲቪሊያንና ሕፃናት ናቸውና ይኼ እንዳይሆን ሠራዊቱ ከትግራይ እንዲወጣ መወሰኑን ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የሠራዊቱ መኖር ለሰብዓዊ ዕርዳታዎች እንቅፋት ፈጥሯል ሲሉ የነበሩ አካላትም፣ አሁን ሠራዊቱ ወጥቷልና ድጋፋቸውን ያድርሱ፡፡ መንግሥትም እነዚህ አካላት ዕውን ድጋፍ ማድረግ ነው ፍላጎታቸው አልያስ ሌላ የሚለውንም የሚያይበት አጋጣሚ ይሆናል›› ብለዋል፡፡

selegna

By selegna

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *