የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ከሚኒስተሮች ምክር ቤት አባልነት ወጥቶ፣ ራሱን ነፃና  ገለልተኛ በማድረግ መቋቋም እንደሚገባው የሕግ ባለሙያዎች ጥያቄ አቀረቡ።

በ2022 ዓ.ም. ኢትዮጵያን የአፍሪካ የፍትሕ ተቋማት ተምሳሌት ለማድረግ የአሥር ዓመት ስትራቴጂካዊ ዕቅዱ ላይ እየመከረ መሆኑን የገለጸው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፣ አሁን ካለበት የመንግሥት አማካሪነትና አስፈጻሚነት ሚናው ሊወጣ እንደሚገባ ተጠይቋል።

ቅዳሜ ጥር 8 ቀን 2013 ዓ.ም. በጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ላይ፣ የኢትዮጵያ ሕግ ባለሙያዎች ማኅበር ውይይት አካሂዷል፡፡

በውይይቱ ተሳታፊ የነበሩት የማኅበሩ አባልና የሕግ ባለሙያ አቶ ዘፋኒያ ዓለሙ፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል ሆኖ ሕግ አርቃቂ ስለሆነ የሚና መደበላለቅ ይታይበታል ብለዋል፡፡

ተቋሙ ከሚያከናውናቸው ሥራዎች አንዱ ጥራቱን የጠበቀ ሕግ ማርቀቅ መሆኑ፣ ነገር ግን በቅርቡ ለምክር ቤት የተመራው የወንጀል ሥነ ሥርዓትና የማስረጃ  ሕግ ፓርላማ ከቀረበ በኋላ፣ በርካታ  አስተያየቶችና ትችቶች እየቀረበበት መሆኑን አውስተዋል፡፡ ይህ ደግሞ እየሆነ ያለው ለምክር ቤቱ ብቃት ያለው ሕግ እየቀረበለት ባለመሆኑ ምክንያት መሆኑን ተናግረዋል።

በተመሳሳይ የውይይቱ ተሳታፊ የነበሩ ሌላ የሕግ ባለሙያ በጠቅላይ ዓቃቤ ማቋቋሚያ አዋጅ ውስጥ፣ ተቋሙ የመንግሥት አማካሪ ተብሎ መገለጹን አስረድተው፣ የበርካታ አገሮች ልምድ ደግሞ እንደዚያ ባለመሆኑ  የአማካሪነት ሚናውን መልቀቅ እንዳለበት አሳስበዋል።

‹‹መንግሥትን እያማከረ በተመሳሳይ ከሳሽ ሆኖ ከፍርድ ቤቶች ጋር መሥራት በጣም አስቸጋሪ ነው፤›› ሲሉ የሕግ ባለሙያው አስረድተዋል፡፡ አክለውም ተቋሙ ላለፉት 27 ዓመታት ሕመም የነበረበትና መንግሥት እንደ ሣሪያ ሲጠቀምበት የነበረ በመሆኑ፣ ‹‹ከሕመሙ እንዲያገግም መሠረታዊ ለውጥ ያስፈልጋል የሚል እምነት አለኝ፤›› ብለዋል።

ከዚህ ጋር በተያያዘ በጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የአሥር ዓመት ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ውስጥ ሕገ ንግሥቱ የሚሻሻልበት መንገድ መቀመጥ አለበት ሲሉ፣ የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያዎች ማኅበር ሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ ቴዎድሮስ ጌታቸው ጠይቀዋል።

ዕቅዱ የሕገ መንግሥቱን አለመተግበር እንደ ፈታኝ ሁኔታ መግለጹን ጠቁመው፣ ‹‹ነገር ግን እንደ ባለሙያ እያልን ያለነው አለመተግበሩ ብቻ ሳይሆን የሕገ መንግሥቱ ተቀባይነትና የመሻሻል ሒደቱ ፈታኝ መሆን ተፅዕኖው ከፍተኛ ነው›› በማለት የመሻሻሉን አስፈላጊነት አስረግጠው ተናግረዋል።

በተለይ አሁን እየታየ ያለውን የሕግ የበላይነት ለማስጠበቅ አለመቻል ክፍተት፣ ከሕገ መንግሥቱ አንፃር በሚገባ መመዘን እንደሚኖርበት ገልጸዋል፡፡

አቶ ቴዎድሮስ ስለዕቅዱ እንዳሉት፣ በትክክል ተግባራዊ ከተደረገ ደፊት የሚፈለገውን ለውጥ ለማምጣት ተስፋ የሚጣልበት ነው። ይሁን እንጂ አሁን እየታየ ያለውን አገራዊ ችግር በመተንተን ማየትና ማካተቱ ፋይዳው የበለጠ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡

ይህ በ2022 ዓ.ም. አገሪቱን የአፍሪካ የፍትሕ ተቋማት ተምሳሌት እንድትሆን ራዕይ ያለው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፣ ሦስት የትኩረት መስኮችን አመላክቷል፡፡ በዋነኛነትም የላቀ የሕግ ተፈጻሚነት፣ የላቀ የፍትሕ አገልግሎትና የተቋም ግንባታ እንደሆኑ አስታውቋል፡፡

ለአብነት  በ2013 ዓ.ም በወንጀል የተገኘና ከአገር የሸሸ ሀብት የማስመለስን አቅም 50 በመቶ ለመድረስ  ተቋሙ እየሠራ እንደሆነ በዕቅዱ የተገለጸ ሲሆን፣ በአሥር ዓመቱ መጨረሻ መቶ በመቶ ለማድረስ መታሰቡ ተመላክቷል።

በተመሳሳይ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በተያዘው ዓመት መጨረሻ የፍትሐ ሔር ፍርድ አፈጻጸም ምጣኔ ወደ 50 በመቶ ለማድረስ እየሠራ እንደሆነ  በስትራቴጂ ዕቅዱ አስታውቆ፣ በ2022 ዓ.ም. ደግሞ ዕቅዱ መቶ በመቶ ለማድረስ እንደሚሠራ ጠቁሟል፡፡

selegna

By selegna

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *