ከድምፃዊ ሃጫሉ ግድያ አስቀድሞ ማንነትን የለየ የማጥቃት አዝማሚያ እንደነበር አስታውቋል

የፀጥታ መደፍረስ በተከሰተባቸው የተለያዩ አካባቢዎች የዘር ማጥፋት ወንጀል ምልክቶች መስተዋላቸውንና መንግሥት ፈጣን የጥንቃቄ ዕርምጃ ካልወሰደ፣ በኢትዮጵያ ሊፈጸም እንደሚችል፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን አስታወቀ።

ኮሚሽኑ የድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች በተከሰቱ የፀጥታ ችግሮች፣ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መበቶች ጥስቶችን በተመለከተ ያካሄደውን ሰፊ የምርመራ ውጤት ዓርብ ታኅሳስ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ በወቅቱም የድምፃዊውን ግድያ ተከትሎ ምርመራውን ባደረገባቸው አካባቢዎች የዘር ማጥፋት ወንጀልን የሚያሟሉ ድርጊቶች አለመከሰታቸውን አስታውቋል።

የድምፃዊውን ግድያ ተከትሎ ኮሚሽኑ ምርመራ ባደረገባቸው 40 አካባቢዎች የተፈጸሙ የወንጀል ድርጊቶች፣ ጭካኔና ግፍ የተሞላባቸው፣ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎች መሆናቸውን አስታውቋል።

 

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) የምርመራ ሪፖርቱን ይፋ ባደረጉበት ወቅት፣ የድምፃዊ ሃጫሉን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ የተፈጸመውም ሆነ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በተከሰቱ የፀጥታ ችግሮች የተስተዋሉ የግፍና የጭካኔ ወንጀሎች፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል የመከሰት አደጋን የሚያሳዩ ምልክቶች ናቸው ብለዋል።

‹‹ኮሚሽኑ እስካሁን በተከታተላቸው የፀጥታ ችግሮች፣ ጭካኔና ግፍ የተሞላባቸው ወንጀሎች ቢፈጸሙም፣ የዘር ማጥፋት ወንጀልን የሚያቋቁሙ ናቸው ብሎ አያምንም፤›› ያሉት ኮሚሽነሩ፣ ነገር ግን እየታዩ ያሉ ጭካኔ የተሞላባቸው የወንጀል ድርጊቶች፣ የዘር ማጥፋት ወንጀል አደጋ ምልክቶች ናቸው ብለዋል።

በመሆኑም መንግሥት ጭካኔና ግፍ የተሞላባቸው ወንጀሎችን ለመከላከል፣ ብሔራዊ ስትራቴጂ ቀርፆ መንቀሳቀስ እንዳለበት ምክረ ሐሳብ መቅረቡን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ምርመራ በ40 የኦሮሚያ አካባቢዎች ባሰባሰበው መረጃ መሠረት፣ የድምፃዊውን ሞት ተከትሎ በነበሩት ሦስት ተከታታይ ቀናት በተከሰተው የፀጥታ መደፍረስ፣ በአጠቃላይ የ123 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ፣ ቢያንስ በ500 ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት ደርሷል፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከመኖሪያቸው መፈናቀላቸውን፣ በግለሰቦች፣ በንግድ ድርጅቶችና በመንግሥት ንብረቶች ላይ ከፍተኛ ውድመትና ዘረፋ መፈጸሙን አስታውቋል።

ሕይወታቸው ካለፈው ሰዎች ውስጥ 35 ያህሉ በሁከቱ በተሳተፉ ግለሰቦችና ቡድኖች የተገደሉ መሆናቸውን፣ እነዚሁ አካላት በ306 ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት ማድረሳቸውን፣ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ዕርምጃ ደግሞ ቢያንስ 76 ሰዎች መገደላቸውንና ከ190 በላይ ሰዎች የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው አስታውቋል።

በሌላ በኩል በፀጥታ መደፍረሱ ወቅት በተከሰተ ፍንዳታ፣ ቃጠሎና መሰል አደጋዎች 12 ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉን ገልጿል። ‹‹በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት የተሳተፉት ብዙ ቁጥር ያላቸው ከቦታ ቦታ በቡድን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች ሲሆኑ በጩቤ፣ በድንጋይ፣ በእሳት፣ በኤሌክትሪክ ገመድ፣ በዱላ፣ በዶማ፣ በገጀራና በመጥረቢያ ሰዎችን ደብድበዋል፣ የአካል ጉዳት አድርሰዋል፣ ፍፁም ግፍና ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በማሰቃየት ወይም በማረድ ጭምር ሰዎችን ገድለዋል፤›› ሲሉ ዳንኤል (ዶ/ር) ተናግረዋል።

አጥቂዎቹ ግለሰቦችና ቡድኖች የነዋሪዎችን ቤት በመስበርና በመግባት ከፊሎቹን በየቤታቸው፣ ከፊሎቹን ከቤታቸው አስገድዶ መንገድ ላይ በማስወጣት እንደገደሉና አስከሬናቸውን መሬት ላይ በመጎተትና ጎዳና ላይ በመጣል ለሰዓታት ሳይነሳ እንዲቆይ ማድረጋቸውንም ጠቁመዋል።

የአካል ጉዳት ከደረሰባቸው ሰዎች ውስጥ መላ አካላቸው በመሰባበሩ ሥቃይ በተሞላበት ሁኔታ በሕክምና ላይ ያሉ ሰዎች እንደነበሩ፣ ከፍተኛ ድብደባ ደርሶባቸው ከሞት የተረፉት አብዛኞቹ ሰዎች አጥቂዎቹ እንደ ገደሏቸው በማመን ጥለዋቸው የሄዱ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

አጥቂዎቹ ከፈጸሙት ድብደባ፣ ግድያና ንብረት ማውደም በተጨማሪ፣ ተጎጂዎችንና የተጎጂ ቤተሰቦችን ብሔርን መሠረት በማድረግ ሲሳደቡ፣ ሲያንቋሽሹ፣ ሲያስፈራሩና ሲዝቱባቸው እነደነበርና ይህም ሰላማዊ ነዋሪዎች በብሔራቸው ወይም በሃይማኖታቸው ምክንያት ለጥቃት የመጋለጥ ከፍተኛ ሥጋትና የሥነ ልቦና ጭንቀት እንደፈጠረባቸው ኮሚሽኑ በምርመራው ማረጋገጡን ገልጸዋል።

በሰው ሕይወትና አካል ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ 6,468 ሰዎች በቤትና በንብረታቸው ላይ በተፈጸመ ጥቃት ወይም ለደኅንነታቸው በመሥጋት ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው በቤተ ክርስቲያንና በመንግሥት ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያዎች ይገኙ እንደነበር የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ በንብረት ላይ ከፍተኛ ውድመት ደርሷል ብለዋል፡፡ መኖሪያ ቤቶችን፣ ንግድ ቤቶችን፣ የግልና የመንግሥት ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ከ900 በላይ የሚሆኑ ንብረቶች በቃጠሎ መውደማቸውንና መዘረፋቸውን በምርመራ ቡድኑ መረጋገጡን አስታውቀዋል።

ኮሚሽኑ ባደረገው ምርመራ መሠረት የድምፃዊ ሃጫሉን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ አካባቢዎች በጥቃቱ በተሳተፉ ሰዎችና ቡድኖች፣ በሲቪል ሰዎች ላይ የተፈጸሙት ጥቃቶች በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ባህርያትን የሚያሟሉ መሆናቸውን ተናግረዋል።

‹‹የጥቃቱ ባህሪና መጠን እንደ አካባቢው ሁኔታ የሚለያይ ቢሆንም፣ በአመዛኙ የክርስቲያን እምነት ተከታዮች በብዛት በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ጥቃቱ በአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ ያነጣጠረ ሲሆን፣ የእስልምና እምነት ተከታዮች በብዛት በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ደግሞ በኦሮቶዶክስ እምነት ተከታዮች ላይ ያነጣጠረ ነበር፤›› ብለዋል።

በአብዛኛው በቡድን የተደራጁ ሰዎች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ በርካታ ሲቪል ሰዎችን በአሰቃቂ ሁኔታ መግደላቸውን፣ ጥቃቱ ያነጣጠረውም በከፊል ብሔርና ሃይማኖታቸው ተለይተው የተመረጡ ሰዎችን ከየቤታቸው ለይቶ በማሳደድና በማጥቃት፣ በከፊል ብሔርና ሃይማኖት ሳይለይ ሰላማዊ ነዋሪዎችን ወይም ሲቪል ሰዎችን ሆን ብሎ በማጥቃት እንደነበር ያስታወቁት ኮሚሽነሩ፣ የወንጀል ድርጊቱ ሥልታዊና የተቀናጀ እንደነበር ጠቁመዋል።

‹‹በጥቃቱ ወቅት በማኅበራዊ ሚዲያና በተወሰኑ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ይተላለፉ ከነበሩት መልዕክቶችና በወንጀል ድርጊቱ ይሳተፉ የነበሩ ቡድኖች ያሰሟቸው ከነበሩት መፈክሮች አንፃር፣  በወንጀል ድርጊቱ የነበሩት ሰዎች ተግባራቸው ሥልታዊና የተቀናጀ ወይም የሰፊ ጥቃት አካል መሆኑን በማወቅ የተሳተፉበት ነበር፤›› ብለዋል።

ጥቃቱን ለማስቆም የፀጥታ አካላት የነበራቸው ሚና ከቦታ ቦታ የተለያየ መሆኑን፣ በተወሰኑ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሉ ቅድመ ዝግጅት በማድረጉ ጉዳቱን ለመከላከል፣ ለማስቆም ወይም ለመቀነስ ተችሏል ብለዋል። በአንፃሩ የፀጥታ አካሉ የወንጀል መከላከል ወይም የማስቆም አቅምና ዝግጁነት ዝቅተኛ በነበረባቸው አካባቢዎች በተለይም በባቱ፣ በሻሸመኔ፣ በጭሮ፣ በሃሮማያ፣ በወሊሶ፣ በአዳማ፣ በጎባ፣ በአርሲ ነጌሌና በአርሲ ሮቤ፣ እንዲሁም በዴራ፣ በአዳባ፣ በአጋርፋ፣ በኮፈሌ፣ በጀጁና በኢተያ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን አስታውቀዋል።

በእነዚህ ከፍተኛ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ጥቃት በሚፈጸምበት ወቅት፣ የአካባቢው ሕዝብና ተጎጂዎች የአካባቢው አስተዳደርና የፀጥታ አካላትን በተደጋጋሚ ዕርዳታ ቢጠይቁም አዎንታዊ ምላሽ አለማግኘታቸውን፣ ይልቁንም ‹‹በበላይ አካል አልታዘዝንም፣ የግለሰብ ንብረት ጠብቁ አልተባልንም፣ የምንጠብቀው የመንግሥት የልማት ተቋማትን፣ ባንኮችንና የሃይማኖት ተቋማትን ነው፤›› የሚል ምላሽ ሲሰጣቸው እንደነበር ለኮሚሽኑ መርማሪዎች ማስታወቃቸውን ገልጸዋል።

በተወሰኑ ቦታዎች ፖሊስ ጥቃቱን እያየ በዝምታ ማለፉን፣ ጥቃቱ የደረሰባቸው ነዋሪዎችና ምስክሮች በከፍተኛ ቅሬታ ለኮሚሽኑ መግለጻቸውን፣ አንድ ተጎጂ ሁኔታውን ለኮሚሽኑ በምሬት ሲገልጹ ‹‹መንግሥት ያለ አይመስልም ነበር›› ማለታቸውን ኮሚሽነር ዳንኤል (ዶ/ር) ተናግረዋል።

ምንም እንኳን የፀጥታ ኃይሉ በየቦታው የገጠመው መጠነ ሰፊ የፀጥታ መደፍረስ ችግርና የፀጥታ አባላቱ የሕይወት መስዋዕትነት በሚጠይቅ ሁኔታ በመሰማራታቸው፣ ኃላፊነታቸው እጅግ ፈታኝ የነበረ መሆኑን መገንዘብ ቢቻልም፣ በተወሰኑ ቦታዎች የነበረው የኃይል አጠቃቀም ተመጣጣኝነት ከፍተኛ ጥያቄ የሚያስነሳ እንደነበርም አስረድተዋል።

ኮሚሽኑ የድምፃዊ ሃጫሉ ግድያን ተከትሎ በተፈጸመው ጥቃት የተሳተፉ አካላትን በመለየት፣ በሕግ እንዲጠየቁ ማድረግ እንደሚገባ፣ ለኦሮሚያ ክልልና ለፌዴራል መንግሥት ምክረ ሐሳብ ማቅረቡን አስታውቀዋል።

selegna

By selegna

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *