ወጣቶች በተለያዩ ምክንያቶች ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ሲፈናቀሉ፣ ከመካከለኛው ምሥራቅ ሕዝቦች ከስደት ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ፣ መንግሥት የተለያዩ አማራጮችን እየወሰደ ቢገኝም፣ አሁንም በከተሞች ላይ የሥራ ዕድል ጫና እየፈጠረ መሆኑ ተገለጸ፡፡

በሥራ ፈጠራ ኮሚሽን የኮሙዩኒኬሽንና የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ ወ/ት ተወዳጅ እሸቱ ለሪፖርተር እንደገለጹት ከሆነ፣ በአገሪቱ ውስጥ ሥራና ሥራ ነክ የሆኑ አጀንዳዎችን የሚመራውና የሚያስተባብረው ተቋማቸው፣ በማኅበረሰቡ እምብዛም ትኩረት ያልተሰጠባቸውን አካላት ማለትም ከስደት ተመላሾችን፣ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮችንና የአካል ጉዳተኞችን መሠረት ያደረገ ሥራ እያከናወነ ነው፡፡

ሰዎች ወደ ከተማ በሚመጡበት ጊዜ ከሥራ ፍለጋ ባሻገር ልዩ ልዩ ፍላጎቶችን ይዘው እንደሚመጡ የገለጹት ወ/ት ተወዳጅ፣ ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእነሱ የሚሆን ፕሮግራም መንደፍ አስፈላጊ መሆኑን በመረዳት እየተሠራበት እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

ኮሚሽኑ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር ‹‹ኢትዮጵያን ማስቻል›› የሚባል ፕሮግራም ቀርፆ ወደ ሥራ እየገባ እንደሚገኝም አስታውቀዋል፡፡ ‹‹ፕሮግራሙ ለአምስት ዓመታት የሚተገበርና ጊዜው የሚጠይቃቸውን ሥራዎች ለእነዚህ አካላት እየፈጠረ እንደሚቆይ ወ/ት ተወዳጅ አብራርተዋል፡፡

ለሥራ ዕድል ተብሎ በየዓመቱ ለሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ባላቸው ፀጋ፣ የሕዝብ ብዛት፣ የወጣቶች ቁጥርና ኢኮኖሚያቸው በሚፈቅድላቸው መጠን የሥራ ዕድሎችን የማመቻቸት ሒደት የሚፈጠር መሆኑን፣ ለዚህ ተብሎ የሚበጀተው በጀት ለታለመለት ዓላማ መዋሉን መቆጣጠር፣ ለአንድ ተቋም ብቻ የሚሰጥ ኃላፊነት አይደለም ብለዋል፡፡

ዜጎች ለሥራ ፈጠራ ብር ተበድረው በሚወስዱበት ጊዜ ጥሩ ስሜት ሊኖራቸው እንደሚገባ የሚያሳስቡት ወ/ሪት ተወዳጅ፣ የተወሰዱ ብድሮች በአግባቡ ካልተመለሱ አመኔታ ማጣትም ብቻ ሳይሆን ሌሎች ብድር ለሚጠብቁ ዜጎች መንገድ ይዘጋል ብለዋል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘም የኢትዮጵያ ጆብስ ዶትኔት የንግድ ክፍል የሆነው ደረጃ ዶትኮም ከሥራ ዕድል ፈጠራ ኮሚሽን ጋር በመተባበር፣ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን በተገኘ ድጋፍ የበይነ መረብ በዓውደ ርዕይ ለሰባት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ለሁለተኛ ጊዜ አዘጋጅቷል፡፡

ቀጣሪ ድርጅቶች የሚያስቀምጧቸውን የሥራ ላይ መሥፈርቶች አሟልተው የሚቀርቡ ተመራቂ ተማሪዎችን ለማብቃት ደረጃ ዶትኮም ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን የደረጃ ዶትኮም ፕሮግራም ዳይሬክተር ወ/ት ሲሃም አየለ አስታውቀዋል፡፡ ደረጃ ዶትኮም በበይነ መረብ ዓውደ ርዕይ ተመራቂ ተማሪዎችን ከቀጣሪዎች ጋር የማገናኘት፣ ለሥራ ቦታዎች ማመልከትና ቀጣሪን ከተመራቂው ጋር በጽሑፍና በቪዲዮ የማገናኘት ሥራ እስከ ኅዳር 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ እንደሚያከናውን ዳይሬክተሯ ሱሳን ጨምረው አስታውቀዋል፡፡

selegna

By selegna

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *