የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክርቤት የእንባ ጠባቂና ግልግል ዳኝነት ፓናል በይፋ ሥራ መጀመሩን ዛሬ ጥቅምት 21 ቀን 2013 ዓም በካፒታል ሆቴል ባደረገው ስብሰባ ይፋ አደረገ።
ምክር ቤቱ እንደገለጸው የእንባጠባቂና ግልግል ዳኝነት ፓናሉ 18 አባላት አሉት። የምክርቤቱ ሰብሳቢ አቶ አማረ አረጋዊ እንደገለጹት፣ ፓናሉ የተቋቋመው ከበርካታ ዓመታት ትግል በኋላ ነው። መንግስት የግልግል ዳኝነት ለማቋቋም ከ15 ዓመታት በፊት ተነሳስቶ የነበረ ቢሆንም፣ የዚህ ዓይነት ተቋም በመንግስት ሊቋቋም እንደማይገባ በመግለጽ ሲከራከሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።
ፓናሉ ከመገናኛ ብዙኃን ጋር ተያይዞ የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት እንዲረዳ የተቋቋመ መሆኑንም አክለዋል።
የፓናሉን አባላት አመራረጥና ኃላፊነታቸውን በተመለከተ ማብራሪያ የሰጡት ሌላው የአስመራጭ ኮሚቴ አባሉ አቶ አብዱ አሊ ሂጄራ ሲሆኑ”ይህ ፓናል እንደ ክብር ዳኝነት የሚታይ ሲሆን በዋናነት የስነምግባር ጥሰትን የሚመለከትና አባላቱም ፍጹም ከመገናኛ ብዙኃን ኢንዱስትሪ ውጭ ናቸው” ብለዋል። አባላቱ ከሚዲያ ሥራ ውጭ ከመሆናቸውም ባሻገር፣ በእጩነት እንኳን የተመረጡት ከምክር ቤቱም ሆነ ከሌሎች ሚዲያዎች ተቋማት ውጭ በሆኑ ግለሰቦች ተጠቁመው መመረጣቸውን አቶ አብዱ አብራርተዋል።
በትውውቅ መድረኩ ላይ የተገኙት የብሮድካስት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ድንቁ(ዶ/ር) ” መገናኛ ብዙኃን እዚህ ላይ መድረሱ በልም ሆነ በተቋምም የሚያስደስት ነው። ፓናሉ መቋቋሙም ለባለስልጣኑም አጋዥ ነው” ብለዋል።
የግልግል ዳኝነቱ በሚዲያ የሚፈጠሩ የሥራ ላይም ሆነ የስነምግባር ግድፈቶችን የሚከላአል መሆኑንና ሚዲያዎች የሚመኙትን ያህል በነፃነትና በገለልተኝነት እንደሚሰሩና መንግስትም በምንም ዓይነት ሁኔታ ጣልቃ እንደማይገባባቸው እምነታቸው መሆኑን ጌታቸው (ዶ/ር) ተናግረዋል።