የተራቀቁ የኮምፒውተር ቫይረሶች በስፋት ጥቅም ላይ የሚውሉ የቀጣዩ ዘመን ስለላ ቁልፍ መሳሪያ እንደሚሆኑ ቴክኖሎጂስቶች ይተነብያሉ። ይሁንና በግዙፍ ኩባንያዎችና መንግስታት ተመራጭ የስለላ ግብዓቶች የሚሆኑት እነዚህን ቫይረሶች ጥቅም ላይ የማዋል ጉዳይ የቁጥጥር መፍትሄ ካልተበጀላቸው የትልልቅ ጦርነቶች መነሻ ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ስጋትን ይዟል።
በአለም በኢኮኖሚ አቅማቸው እጅግ ደካማ ከሚባሉት አገሮች አንስቶ ፈርጣማ አቅማቸውን ተጠቅመው የረቀቁ ስልቶችን እስከሚጠቀሙት ድረስ ስለላ ለዘመናት በአገራት የኖረ አሁን ደግሞ እጅግ ውስብስብ ሆኖ የቀጠለ የደህንነት ማረጋገጫ አንድ ስልት ነው። የቀድሞው ዘመን የስለላ መኮንኖች ረጅም ጊዜን የሚፈጁ የአካልና አዕምሮ ቅልጥፍናን በሚያጎናጽፉ የረቀቁ ስልጠናዎች አልፈው ወደ ስራ ይሰማራሉ። ሚስጥርን አነፍንፎ ለማግኘት ህይወታቸውን አደጋ ላይ እስከመጣል የሚደርስ መስዋዕትነትንም ይከፍላሉ። በታሪክ ተመዝግበው የሚገኙና ሰላዮች ድንበር እና ጥብቅ የደህንነት ስርዓቶችን ለማለፍ ሲሞክሩ የተያዙባቸው በእድሜ ልክ ጽኑ እስርና በሞት የተቀጡባቸው ታሪኮች በርካታ ናቸው።
አንዳንዶቹም መያዛቸው እርግጥ መሆኑን ሲያውቁ ራሳቸውን ወዲያው የሚያጠፉባቸው ጊዜያት ብዙ ናቸው። አሁን ግን የስለላ መኮንኖች በአካል አገራትን እያቋረጡ ወሳኝ የደህንነት እና ውድድር መረጃዎችን ለማግኘት አደጋ የሚጋፈጡበት፣ ፋይሎችና በድብቅ ለማውጣት መከራ የሚያዩበት ዘመን እየቀረ ይመስላል። ረቂቅ ቫይረሶችን ወደተለያዩ አገራት የኢንፎርሜሽንና ኮሚኒኬሽን ስርዓት ውስጥ በማስረግ ቁልፍ መረጃዎችን ፈልፍሎ ማውጣት ተጀምሯል። በ2010 በአሜሪካውያና እስራኤላውያን የተሰራ ነው የተባለው ስታክስኔት የተሰኘ የኮምፒውተር ፕሮግራም በኢራን የኒውክሊየር ተቋም ላይ ጉዳት ላይ ማድረሱ ሲሰማ ነበር አለም ለጉዳዩ ትኩረትን መስጠት የጀመረው። ከዚያም በተለያዩ አገራትና ኩባንያዎች ኔትወርኮች ላይ ጥቃት ያደረሱት ፍሌም፣ ሬድ ኦክቶበር፣ ዳርክሆቴል የተሰኙ እና ሌሎች ቫይረሶች የጉዳዩን አሳሳቢነት እያጎሉት መጥተዋል።
በታሪክ ተመዝግበው የሚገኙና ሰላዮች ድንበር እና ጥብቅ የደህንነት ስርዓቶችን ለማለፍ ሲሞክሩ የተያዙባቸው በእድሜ ልክ ጽኑ እስርና በሞት የተቀጡባቸው ታሪኮች በርካታ ናቸው።
የመረጃ አነፍናፊ ቫይረሶቹ ምን እንደሚፈለግ በግልጽ እንዲያውቁ ተብለው የሚሰሩ ስለሆነ አብዛኛውን ጊዜ ወደ ኔትወርኩ መግባታቸው ሳይታወቅ የተላኩበትን ብቻ ነጥለው ላሰማሯዋቸው አገራት ወይም ኩባንያቸው ያደርሳሉ። በተለይ የተጠናከረ የመረጃ እና ኔትወርክ ደህንነት የሌላቸው ተቋማት ለዚህ መሰሉ ጥቃት የተጋለጡ ናቸው።